
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ለመወዳደር ለተመዘገቡ የግል ዕጩ ተወዳዳሪዎች ነፃ የአየር ሰዓት ድልድል ይፋ አደረገ።
ቦርዱ በምርጫው በግል ዕጩነት ለመወዳደር የተመዘገቡ የግል ዕጩ ተወዳዳሪዎችን አወያይቷል።
ነፃ የአየር ሰዓት ድልድሉ ለየአንዳንዱ ወንድ የግል ዕጩ 15 ደቂቃ ርዝማኔ ያለው አንድ የቴሌቪዥን፣ አንድ የሬዲዮ እና አንድ የጋዜጣ ዐምድ በመረጧቸው መገናኛ ብዙኃን ላይ እንዲያስተላልፉ ያደርጋል።
የግል ዕጩዋ ሴት ስትሆን በሦስት የመገናኛ ብዙኃን የሥርጭት አማራጮች የሚሰጠው ነፃ የአየር ሰዓት ድልድል በመረጠችው የሥርጭት አማራጭ አንድ ተጨማሪ ዕድል ይሰጣል።
ሴት ሆና አካል ጉዳተኛ ስትሆን ደግሞ ተጨማሪ ዕድሉ ወደ አምስት ጊዜ ከፍ ይላል።
ይኸው ድልድል ዕጩው ወንድ አካል ጉዳተኛ ሲሆን፤ በሦስት የሥርጭት አማራጮች ለአንድ ጊዜ የነበረው ነፃ የአየር ሰዓት ድልድል በመረጠው የሥርጭት አማራጭ ላይ አንድ ተጨማሪ ዕድል ይሰጣል።
የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ቦርዱ ምርጫው በጊዜ ሠሌዳው መሠረት ለማካሄድ የቅድመ-ምርጫ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።
የግል ዕጩ ተወዳዳሪዎች ነፃ የአየር ሰዓት ድልድልም የዚሁ አካል መሆኑን ተናግረዋል።
የግል ዕጩዎቹ በሚያደርጉት የምረጡኝ ቅስቀሳ ወቅት ሕጉን ተከትለው በኃላፊነት ስሜት መሆን እንዳለበትና ይህም የምርጫውን ሰላማዊ፣ ፍትሐዊና ተዓማኒነት በማረጋገጥ ረገድ ድርሻ እንዳለው አመልክተዋል።
ለግል ዕጩዎቹ አጠቃላይ የምርጫ የሕግ ማዕቀፎች፤ ቦርዱ በቅድመ-ምርጫ ወቅት የሠራቸውን ተግባራትና አስመልክቶ በኃላፊዎች ገለጻ መደረጉን ከቦርዱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የምርጫ ቅስቀሳ ሥነ-ምግባር፣ ነፃ የአየር ሰዓት አጠቃቀምና ድልድልን እንዲሁም ለዕጩዎች ስለሚከፋፈለው የገንዘብ ድጋፍ በተመለከቱት መመሪያዎች ደግሞ ማብራሪያ ተሰጥቷቸዋል።
ተሣታፊዎቹ በቀረቡት ገለጻዎች ላይ እንዲሁም ባጠቃላይ ከምርጫው ጋር ተያያዥነት ያላቸው ጥያቄዎችን ላነሷቸው ጥያቄዎችና አስተያየቶች ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።
0 አስተያየቶች
ገና አስተያየት የለም። የመጀመሪያው አስተያየት ሰጪ ይሁኑ!