
አገር በቀል ዕውቀትን ለማኅበራዊ ትስስር፣ ለዘላቂ ሰላምና ለኢኮኖሚ ግንባታ ያላቸውን ፋይዳ ለማጎልበት እየተሰራ መሆኑን የባህልና ስፖርት ሚኒስቴርና በዘርፉ የሚንቀሳቀሱ አካላት ገለጹ፡፡
አገር በቀል ዕውቀት አንድ ማኅበረሰብ ከአካባቢው ጋር ባለው የረጅም ጊዜ ግንኙነት የሚያዳብረው፣ በትውልድ ቅብብሎሽ የሚተላለፍና ለችግር መፍቻነት የሚያገለግል ጥበብ ነው።
በኢትዮጵያ አገር በቀል ዕውቀት እንደ "እድር" እና "እቁብ" ያሉ የኢኮኖሚ ዋስትናዎችን፣ እንደ "ሸንጎ" ያሉ ባህላዊ የዳኝነት ሥርዓቶችን እንዲሁም በርካታ ዕውቅና ያገኙ ጥበቦችን ያካትታል።
ጥበቦቹ ለዘላቂ ልማት መሠረት ከመሆናቸውም በላይ ፤ማኅበረሰቡ ችግሮቹን በራሱ አቅምና ፍልስፍና ለመፍታት ያስችሉታል።
የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነፊሳ አልማህዲ እንደሚገልጹት፤ ሚኒስቴሩ አገር በቀል ዕውቀትን በ10 ዋነኛ ዘርፎች በመከፋፈል እየሰራ ነው፡፡
ዘርፎቹ የባህል መድኃኒትን፣ ባህላዊ የሽምግልና ሥርዓቶችን፣ የባህል ምግቦችንና ሌሎችንም የፈጠራ ጥበብን እንደሚያካትት ለኢዜአ ገልጸዋል፡፡
ከማኅበራዊ ፋይዳቸው ባለፈ የሥራ ዕድል በመፍጠርና የገቢ ምንጭ በመሆን ለኢኮኖሚ ግንባታ እንደሚያበረክቱ ያመለከቱት ሚኒስትር ዴኤታዋ፣ሚኒስቴሩም የልማት ሥራ እያከናወነ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ባሕሎች አካዳሚ ምክትል ዳይሬክተር ደሳለኝ አምሳሉ (ዶ/ር) ማኅበረሰቡ ለዘመናት ሲጠቀምባቸው የቆዩት የግጭት መፍቻ ሥርዓቶችና የዕፅዋት መድኃኒት ቅመማ ከዘመናዊው ሥርዓት ጋር ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
"ቡልኮ" የተሰኘ የአገር በቀል ዕውቀት ጥናትና ምርምር መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ አብዱልፈታህ አብድላህ፤ አገር በቀል ዕውቀት ለዛሬው ሕይወታችን መሠረት መሆናቸውን ይናገራሉ።
ዕሴቶቹን ከዘመናዊው የትምህርት ሥርዓት ጋር በማቆራኘት ለትውልድ ለማሻገር እየተሠራ መሆኑንም አስረድተዋል።
0 አስተያየቶች
ገና አስተያየት የለም። የመጀመሪያው አስተያየት ሰጪ ይሁኑ!