.jpg&w=2048&q=75)
ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የወርቅ ጌጣጌጥ ሰርቃ የተሰወረችው ግለሰብ 24 ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በቁጥጥር ሥር መዋሏን የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ገለጸ፡፡
ተጠርጣሪዋ የስርቆት ወንጀሉን የፈፀመችው በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9 ልዩ ቦታው ጦር ኃይሎች ኩዊንስ ሱፐር ማርኬት አካባቢ ከሚገኝ አንድ መኖሪያ ቤት ውስጥ ነው።
ተጠርጣሪዋ ከዚህ ቀደም ከግል ተበዳይ ጋር ትውውቅ ያላት ሲሆን፤ የግል ተበዳይም ቤቷን ዘግታ ወደ ሥራ በሄደችበት አጋጣሚ የበር ቁልፍ ገንጥላ ትገባለች፡፡
ከዚያም ቁም ሳጥን ውስጥ ተቀምጦ የነበረ ሰባት ግራም ባለ 21 ካራት የጣት ቀለበት፣ 14 ግራም ባለ 21 ካራት የእጅ ብራስሌት፣ 10 ግራም ባለ 21 ካራት የአንገት ሀብል ወስዳ ትሰወራለች፡፡
የሰረቀቻቸው ከወርቅ የተሰሩት ጌጣጌጥ ጠቅላላ ዋጋ አንድ ሚሊዮን 23 ሺህ ብር ይገመታሉ ይላል መረጃው፡፡
ንብረታቸው የተሰረቀባቸው የግል ተበዳይም ጉዳዩን በቀራንዮ ክፍለ ከተማ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ለአጉስታ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ ያመለክታሉ።
ወንጀሉ ሲፈፀም ምንም ዓይነት ማስረጃ ባለመኖሩ ተጠርጣሪዋን ለመያዝ ከባድና ውስብስብ ቢያደርገውም፤ ፖሊስ የምርመራና ክትትል ቡድን በማቋቋም ወንጀሉ ማን ፈፀመው በሚል ምረመራውን ይጀምራል፡፡
በዚህም ፖሊሳዊ የምርመራ ስልትና ጥበብን ተጠቅሞ ባደረገው ብርቱ ክትትል ግለሰቧን 24 ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በቁጥጥር ሥር ማዋል እንደተቻለ ከክፍለ ከተማው ፖሊስ መምሪያ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ተጠርጣሪዋ በቁጥጥር ሥር ከዋለች በኋላ ከተሰረቁት ውስጥ ሁለት የጣት ቀለበቶች ተገኝተዋል፡፡የአንገት ሃብልና የእጅ ብራስሌት የት እንደሸጠችው በተከናወነ ምርመራ በአጭር ጊዜ ውስጥ ወርቁንና የተሸጠበትን 500 ሺህ ብር ማስመለስ ተችሏል።
የተሰረቁ ንብረቶችን ሙሉ በሙሉ በማስመለስ በተጠርጣሪዋ ላይ አስፈላጊው ምርመራ በመጣራት ላይ እንደሚገኝ ጠቅላይ መምሪያው አስታውቋል፡፡
ኀብረተሰቡ ውድ ንብረቶችን ለወንጀል ፈፃሚዎች ምቹ ሁኔታን በሚፈጥር ሁኔታ ማስቀመጥ እንደሌለበት ያሳሰበው ጠቅላይ መምሪያው፣ወንጀል ፈፃሚዎች ወንጀል ፈፅመው ለጊዜው ቢሰወሩም በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ጥቆማ ከመስጠት ጀምሮ ለፀጥታ አካላት እያደረገ ያለውን ትብብር እንዲያጠናክር ጠይቋል።
0 አስተያየቶች
ገና አስተያየት የለም። የመጀመሪያው አስተያየት ሰጪ ይሁኑ!