እሑድ 19 ኤፕሪል 2026
05:09:44 ከሰዓት UTC+3 - Addis Ababa
ኢኮኖሚ

ዋይልድቤሪስ ኩባንያ በኢትዮጵያ በይፋ ሥራ ጀመረ

2 ደቂቃ ንባብ
ዋይልድቤሪስ ኩባንያ በኢትዮጵያ በይፋ ሥራ ጀመረ
የአገር ውስጥ አምራቾችን በቀጥታ ዓለም አቀፍ ሸማቾች ጋር ለማገናኘት እንደ ዲጂታል ኮሪደር ሆኖ የሚያገለግለው ታዋቂው የሩሲያ የኦንላይን የገበያ መድረክ ወደ ሥራ ገብቷል፡፡
1 / 2
ኢትዮጵያ ለኢ-ኮሜርስ ዘርፍ ልዩ ትኩረት በመስጠት የሎጅስቲክስ፣ የክፍያና የማርኬቲንግ ሥርዓቶችን በማቀናጀት ንግድን በዲጂታል መሠረተ ልማት አማካይነት ለማሳደግ እየሰራች መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስታወቀ።

"ዋይልድቤሪስ" ኩባንያ በኢትዮጵያ በይፋ ሥራ ጀምሯል፡፡

በዘርፉ በተጀመረው አዲስ ምዕራፍ፤ የአገር ውስጥ አምራቾችን በቀጥታ ዓለም አቀፍ ሸማቾች ጋር ለማገናኘት እንደ ዲጂታል ኮሪደር ሆኖ የሚያገለግለው ታዋቂው የሩሲያ የኦንላይን የገበያ መድረክ ወደ ሥራ ገብቷል፡፡

በኢትዮጵያ ዛሬ በይፋ ሥራ የጀመረው"ዋይልድቤሪስ" (Wildberries) የተባለው ኩባንያ ነው፡፡

የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ይድነቃቸው ወርቁ  በማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ላይ እንደተናገሩት፤ የዋይልድቤሪስ ወደ ኢትዮጵያ መምጣት በአገሪቱ የንግድ ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው።

ኢ-ኮሜርስ መልክዓምድራዊ መሰናክሎችን በማስወገድ በኢትዮጵያ የተመረቱ ምርቶችን በቀጥታ በዓለም አቀፍ መድረክ ላይ እንዲቀርቡና የአገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ግኝት በማሳደግ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ብለዋል።

እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ፤ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያና የሩሲያ የንግድ ልውውጥ ወደ 400 ሚሊዮን ዶላር እየተጠጋ ቢሆንም የንግድ ሚዛኑ ወደ ሩሲያ ያዘነበለ ነው።

በመሆኑም እንደ ዋይልድቤሪስ ያሉ የዲጂታል መድረኮች የኢትዮጵያን የወጪ ንግድ በማሳደግ ይህንን የንግድ ሚዛን ለማስተካከል ዕድል እንደሚፈጥሩ እምነታቸውን ገልጸዋል የሚለው ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ነው።

ዋይልድቤሪስ በሩሲያ፣ በቤላሩስ፣ በካዛክስታንና በሌሎችም አገሮች ያለውን ሰፊ ተደራሽነት በመጠቀም የኢትዮጵያ ምርቶች አዳዲስ ገበያዎችን እንዲያገኙ ያስችላል ተብሎም ታምኖበታል።

ሚንስትር ዴኤታው ለአገር ውስጥ አምራቾችና ላኪዎች ባስተላለፉት መልዕክት፤ “አሁን የእናንተ ሰዓት ነው” በማለት ዓለም አቀፍ ገበያው በዲጂታል መድረክ አማካይነት እንዲጠቀሙበት አሳስበዋል።

አምራቾች ከኩባንያው ጋር በቅርበት በመስራት፥ የሎጀስቲክስና ዲጂታል ማርኬቲንግ ግንዛቤያቸውን ማሳደግ እንዲሁም ምርቶቻቸውን በጥራትና ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ለዓለም ገበያ እንዲያዘጋጁም አስገንዝበዋል አቶ ይድነቃቸው።

የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ለዋይልድቤሪስና ለሌሎች መሰል የቴክኖሎጂ ተቋማት አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ፤ የኢትዮጵያ ምርቶች በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
ኢኮኖሚዲጂታል ግብይትንግድና ቀጣናዊ ትስስር ማኒስቴር

0 አስተያየቶች

ገና አስተያየት የለም። የመጀመሪያው አስተያየት ሰጪ ይሁኑ!